ቢሮው ለህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች የግንዛቤ ማስጨባጭ ስልጠና ሰጠ፡፡

(አዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ፤ ሰኔ 05/2016ዓ.ም) የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የትራንስፖርት ስትራቴጂና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ እንዲሁም ቅንጅታዊ አሰራርን በተመለከተ ከታክሲ፣ ሀይገር፣ ሜትር ታክሲ፣ የሞተር ሳይክል፣ የጭነት ትራንስፖርት ና አደይ አበባ አገልግሎት ሰጪ ማህበራት ጋር የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና አካሄደ።

የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ወርቁ ደስታ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጡን ማሻሻል ለነገ የማይባል ጉዳይ መሆኑን በመጠቆም፤ በዋናነትም አገልግሎት ሰጪው የከተማውን ስትራቴጂክ ለማስተግበር የሚኖራቸውን አስተዋፅኦ ለማስገንዘብ ስልጠናው ጠቃሚ ነው ብለዋል።

የስልጠናው ሰነድ በትራንስፖርት ዘርፍ አቅም ግንባታ ዳይሬክቶሬት አቶ ኃይለማርያም ተክለሚካኤል እና የህዝብ ትራንስፖርት አደረጃጀትና ኦፕሬሽን ፈቃድ ቡድን መሪ አቶ ይታገሱ ሞገስ ያቀረቡ ሲሆን፤ ቢሮ እየሰራ ያለውን ስራና በትራንስፖርት ስትራቴጂው የተቀመጡ ተግባራትን በዘርፉ ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር መስራት እንደሚገባ ገልፀዋል።

በስልጠናው መድረክም በዋናነት የትራንስፖርት ስትራቴጂን በከተማዋ ለመተግበር የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪው በአገልጋይነት መንፈስ አገልግሎት መስጠት እንደሚጠበቅበትና በዘርፉ ያሉ ማህበራት ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባቸው ተጠቁሟል።

እንዲሁም የህዝብ ትራንስፖርት አደረጃጀትና ኦፕሬተርነት ፍቃድ ባስቀመጠው የአሰራር መመሪያ መሰረት አገልግሎት መስጠት አስፈላጊ ነው ተብሏል።

በመጨረሻም የህዝብ ትራንስፖርት ማህበራት አመራሮችና ተወካዮች ላነሱቸው ጥያቄዋች ዙሪያ የጋራ ውይይት በማድረግ በቀጣይ በጀት አመት በዘርፉ ያሉ አገልግሎት ሰጪዎችን አቅም ለመገንባት ቢሮው ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ ተገልጿል።

ቴሌግራም ቻናል:-https://t.me/transport_bureauhttps://

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/aatb

ነፃ የስልክ መስመር 9417 ይጠቀሙ!

Leave a Reply