መጋቢት 26/2015ዓ.ም ፤ አዲስ አበባ፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን ዛሬ ይፋ ባደረገው የተሽከርካሪ ቴክኒክ ምርመራ መተግበሪያ ሲስተም ከዚህ ቀደም ከተሽከርካሪ አገልግሎት ጋር በተያየዘ ሲስተዋሉ የነበሩ የህገ ወጥ ተሽከርካሪዎች የቴክኒክ ምርመራ ሰርተፊኬት፣ የተሽከርካሪዎች የቴክኒክ ብቃት በወቅቱ አለማስመርመርና ሌሎችም ችግሮችን ለመፍታት የመተግበርያው ሲስተም ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ተገልጿል።

መተግበርያውም በቴዎስ ቴክኖሎጂ የበለፀገና ለአምስት አመት የሚቆይ ሲሆን ፤ ቴክኖሎጂው ከሰዎች ንክኪ ነፃ የሆነ አሰራርን ለመተግበር የሚያስችልና በሞባይል አፕልኬሽን ጭምር የታገዘ ነው ተብሏል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፍሬው ደምሴ የቴዎስ ቴክኖሎጂን በዋናነት ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የሚቆጣጠር እና የሚያስተዳደር መሆኑንና ቴክኖሎጂው አገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን አጋዥ መሆኑን ገልፀዋል።

የቴዎስ ቴክኖሎጂ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቴዎድሮስ አጥናፉ የበለፀገው ቴክኖሎጂ የተሽከርካሪ ቴክኒክ ምርመራ ያደረጉን እና ያላደረጉትን የሚለይ፤ ሀሰተኛ የተሽከርካሪ ቴክኒክ ምርመራን የሚያጋልጥ፤ የተሽከርካሪ የነዳጅ አጠቃቀም በአይነት የሚለይ፤ መረጃ ለባላስልጣን መስሪያ ቤቱ ቋት በቀጥታ የሚልክ መሆኑንና ከተሽከርካሪው ጋር በተያያዘ ጠቃሚ መረጃዎችን በቀላሉ ለማወቅና በዘርፉ የሚሰጥን አገልግሎት ለማዘመን እንደሚረዳ ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም ለሁሉም የተሽከርካሪ ቴክኒክ ምርመራ ተቋማት እና ለባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ባለሙያዎች በአተገባበሩ ዙሪያ ስልጠና እንደሚሰጥና መተግበሪያውንም ከጎግል አፕስቶር በማውረድ መጠቀም እንደሚቻል ኃላፊው አክለው ገልጸዋል።

ከቴዎስ ቴክኖሎጂ ጋር በተደረገው የሶስትዮሽ ስምምነት የፊርማ ስነስርዓት ላይ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ፣ የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን፣ ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ባለድርሻ አካላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳታፊ ሆነዋል።

ምንጭ:-አሽከርካሪ ተሽከርካሪ ኮሙኒኬሽን

Leave a Reply